27/02/2024
ዩኒቨርሲቲው የ2016 ዓ.ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና (Exit Exam) ውጤት ይፋ አደረገ።
-------------------------------------------------------------------
የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት አክበር ጩፎ (ዶ/ር ) የ2016 ዓ.ም አጋማሽ ዓመት የመውጫ ፈተና ውጤትን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል።
በዩኒቨርሲቲው በመደበኛ እንዲሁም በተከታታይ የትምህርት መርሃ ግብሮች ትምህርታቸውን ከተከታተሉ ጠቅላላ ተማሪዎች 312 ያህሉ የ2016 ዓ.ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና ለመውሰድ ብቁ ሆነው መመዝገባቸውን ምክትል ፕሬዝዳንቱ አሳውቀዋል።
በዩኒቨርሲቲው በአስራ ሁለት የትምህርት መስኮች የተሰጠውን የ2016 ዓ.ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና በአጠቃላይ 312 ተማሪዎች መውስዳቸውንም ዶክተር አክበር ጠቁመዋል።
በመውጫ ፈተናው ከተቀመጡ ጠቅላላ ተማሪዎች በድምሩ 78.72 በመቶ ማለፊያውን ነጥብ ማስመዝገባቸውንም ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው ለ2016 ዓ.ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና ተገቢውን ሁለንተናዊ ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ፈተናውን ማስፈተን ችሏል ያሉት ምክትል ፕሬዝዳንቱ ፤ በሂደቱም የከፋ ችግር አላጋጠመንም ብለዋል።
ከዚህ ቀደም ለመጀመሪያ ግዜ ከተካሄደው ሀገር አቀፍ የመውጫ ፈተና አንጻር እንደ ተቋም በ2016 ዓ.ም አጋማሽ መውጫ ፈተና የተሻለ አፈጻጸም ታይቷል ሲሉም ዶክተር አክበር ተናግረዋል።
በዩኒቨርሲቲው በተካሄደ የ2016 ዓ.ም አጋማሽ መውጫ ፈተና በጤና ሳይንስና ሕክምና ኮሌጅ በተለያዩ የጤና ፕሮግራሞች (Medical laboratory 100%, Public health 100%, Midwifery 100%, Nursing 100% እና Pharmacy 97%) ተፈታኞች እጅግ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻላቸው ለአብነት ተጠቃሽ መሆኑንም ምክትል ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።
በቀጣይ ግዜያት ያጋጠሙ ችግሮችን በጥልቀት በመገምገም፣ ተገቢውን የእርምት እርምጃ በመውሰድ እና ምርጥ ተሞክሮዎችን በማስፋት በሁሉም ኮሌጆችና ትምህርት ቤቶች የላቀ ውጤት እንዲመዘገብ በቁርጠኝነት እንሰራለን ብለዋል።
ዶክተር አክበር በመውጫ ፈተናው ማለፊያ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች እንኳን ደስ አላችሁ በማለት መልዕክት ያስተላለፉት ሲሆን ፤ የሚፈለገውን የማለፊያ ውጤት ያላስመዘገቡ ተማሪዎች ቀጣይ ሰኔ ወር መጨረሻ ፈተናውን ዳግም መውሰድ የሚችሉ መሆኑንም አሳውቀዋል።
የ2016 ዓ.ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና የከፋ ችግር ሳያጋጥም እንዲሳካ ድጋፍ እና ክትትል ያደረጉ አስተባባሪዎችን እና ባለድርሻ አካላትንም ምክትል ፕሬዝዳንቱ አመስግነዋል።
የ2016 ዓ .ም አጋማሽ የመውጫ ፈተና ውጤት ከዛሬ የካቲት 18/ 2016 ዓ.ም ጀምሮ ስለተለቀቀ ተፈታኞች በ https://result.ethernet.edu.et ሊንክ ማየት የሚችሉ መሆኑንም አሳውቀዋል።
➭ «ዕውቀትን በተግባር!!»
📷የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት!!
➤ የካቲት 18 /2016 ዓ.ም (ወሶዩ)
◼ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟላ መረጃ ለማግኘት ትክክለኛውን የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ሶሻል ሚዲያ በመቀላቀል ቤተሰብ ይሁኑ🔻
▪Telegram ➲ https://t.me/WolaitaSUniversity
▪Facebook ➲ https://www.facebook.com/profile.php?id=100063820159424
▪YouTube ➲ https://www.youtube.com/channel/UC6VukdZbl5iVgZGXG8BkMdw/videos
Website ➲ http://www.wsu.edu.et/
አብራችሁን ስለሆናችሁ እናመሰግናለን🙏🙏