ሰው ለበጎ የበጎ አድራጎት ማህበር ከስሙ እንደምንረዳው በበጎነት የሚያምን እና በጎዎችን በማብዛት ለበጎ ተግባር የተቋቋመ ማህበር ነው። ከጥቂት ደጋጐች ጋር በመሆን ችላ የተባሉ ማህበረሰባዊ ክፍተቶችን ለመሙላት ያለመ ማህበር ሲሆን ማህበሩ በእቅድ ደረጃ ቀደም ብሎ ምስረታውን ለማረግ ቢያስብም በአንዳንድ ጉዳዮች እና በመንግስት አሠራር ክፍተቶች ምክንያት እውን ባይሆንም በ 2015 ባልተቀናጀ መንገድ በግለሠብ ደረጃ ከደጋግ ደጋፊዎቹ በተደረገ ድጋፍ በበዓል ሰሞን የሚታዩትን ችግሮች መፍትሔ ለማግኘት ሲጥር ከርሟል።
አሁን ግን ድርጅቱን ህጋዊ አድርጐ የሚሠማራበትን ተግባራት በማስፋት የበለጠ ተደራሽ ለመሆን ዝግጅቱን በማጠናቀቅ
ላይ ይገኛል፡፡ ማህበሩ በዋነኝነት ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ቤተሰቦች በዓልን በደስታ እንዲያከብሩ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ፣ ቤተሰባቸውን ያጡ ብሎም ለችግር የተጋለጡ ህፃናትን እንዲሁም አሣዳጊዎች እና ቤተሰቦችን የሙያ ስልጠና እና መነሻ ገንዘብ በመስጠት እራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግ፣ በሰው ቤት ስራተኝነት ትምህርት በመማራቸው ብቻ በዝቅተኛ ደሞዝ ተቀጥረው የሚሰሩ የማታ ተማሪ ሴቶችን ከሚደረስባቸው ጥቃት እንዲሁም የትምህርት ማቋረጥ የሚገፋፏ ምክንያቶችን መቅረፍ እና ማህበረሰቡን በሚጠቅሙ ማህበረሰባዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ተግባራት ላይ መሳተፍ ግቡ አርጐ ለመንቀሳቀስ በከፍተኛ ፍላጎት ወደ ዘርፉ እየገባ ያለ ማህበር ነው።
ሰው ለበጎ ዋና መርሁ ሰብአዊነት ነው። ዘር ፣ ቀለም እና ሃይማኖት ከአላማው ጋር ስለሚጣረሱ ከአሠራሩ ላይ የተወገዱ ናቸው።
የሰው ለበጎ ራዕይ ፦
በአስከፊ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጐች በማህበረሰባዊ ፣ በስነ ልቦና እና በኢኮኖሚያዊ ድጋፍ የአኗኗር ዘይቤያቸው ተቀይሮ እንዲሁም ብቁ ተሳታፊ ዜጐች በማድረግ ከተረጂነት መንፈስ እንደወጡ መረዳት።
የሰው ለበጎ ተልዕኮ ፦
- የማህበረሰቡን የስነ ልቦና ጫና ለመቅፍ የስነ ልቦና እና የመልሶ ማቋቋም ተግባር መስራት
- የሙያ ክህሎት ስልጠና መስጠት
- የሴቶች እና የእናቶች የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የመነሻ ገንዘብ ማቅረብ
- የህፃናት እና ሴቶችን ጥቃት ለመከላከል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ትብብር ማድረግ
የሰው ለበጎ እሴቶች ፦
- ሰብአዊነት
- ግልፅነት
- ሚዛናዊነት
- አለማዳላት
- ተጠያቂነት
- ታማኝነት
ከፈጣሪ ፍቃድ ጋር በ 2016 ሁሉም ነገር አልቆ ወደ ስራ በመግባት ከዚህ በፊት የተሰሩ ተግባራትን መልክ አስይዞ በጎዎችን በመያዝ ወደ ተግባር ለመግባት ያስባል። ለዚህም አላማ ከግብ መምታት የእርሶ ድጋፍ የላቀ መሆኑን እናስገነዝባለን።
"ኑ ነገ ለብዙሃን ተስፋና መጠለያ የሚሆነውን ማህበር በአብሮነት እና በደግነት መንፈስ እንመስርት! "
ራስ አዲሱ ተስፋዬ